አመልድ ኢትዮጵያ 6.8 ሚሊየን ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እያደረገ ነው
አመልድ ኢትዮጵያ በ2015 ዓ.ም ሁለገብ ጥቅም የሚሰጡ 6.8 ሚሊየን ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እያደረገ ነው፡፡ ከተዘጋጁት ችግኞች መካከል 3.255 ሚሊየን የሚሆኑት ሀገር በቀል ሲሆኑ፣3.6 ሚሊየን ደግሞ የውጭ አገር ዝርያ ያላቸው ናቸው፡፡ ችግኞቹ የሚተከሉበት የቦታ ሥፋት 2040 ሄክታር መሬት አስካሁን ተለይተዋል፡፡ የችግኝ መትክያ ቦታዎቹ በወል መሬት፣ በአርሶ አደር ማሣ (ጥምር ግብርና)፣በተቋማት (በአብያተክርስቲያን እና በትምሕርት ቤቶች) ናቸው፡፡ በእነዚህ ቦታዎች 4.8 ሚሊየን የሚሆኑ የችግኝ መትከያ ጉድጓድች ተዘጋጅተዋል፡፡ ከሰኔ 26 ቀን 2015 ጀምሮ የችግኝ ተከላ እንደሚጀመር የአመልድ ኢትዮጵያ የደን፤አካባቢ እና የአየር ንብረት ለውጥ ፕሮግራም ዳይሬክተር አቶ ሰሎሞን አየለ ተናግረዋል፡፡
የችግኝ መትከያ ቦታዎች በዋናነት በምእራብ አማራ አካባቢዎች ማለትም ደራ፣እስቴ፣ሠከላ፣ሊቦከምከም፣ እብናት ቋራ፣ሲሆኑ ምሥራቅ አማራ ደግሞ ዋድላ፣መቄት፣ጋዞ፣ላስታ፣ዳህና፣ጋዝጊብላ፣ እና በሰቆጣ ዙሪያ ናቸው፡፡ በተከዜ ተፋሰስ አካባቢ የሚካሄደው የችግኝ ተከላ እንዲያተኩር የሚፈለገው ውኃገብ በሆኑ አካባቢዎች የፍራፍሬ ልማት እና ሁለገብ ጠቀሜታ ያላቸውን የዛፍ ዝርያዎች ሊጸድቅ በሚችልበት የአርሶ አደሮች ማሣ ላይ ማልማት ይመከራል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የተራቆቱ የወል መሬቶችን ከእንስሳት እና ከሠው ንክኪ ክልሎ መጠበቅ እና ማልማት አዋጭ እና ተመራጭ ዘዴ ነው፡፡
በተከዜ ተፋሰስ አካባቢ የሚደረጉ የችግኝ ተከላ ሥራዎች የሚጸድቁ ዝርያዎችን በሚጸድቁበት ቦታ በመትከል አላስፈላጊ የሀብት ብክነትን ለመቀነስ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን የአመልድ ኢትዮጵያ የደን፤አካባቢ እና የአየር ንብረት ለውጥ ፕሮግራም ዳይሬክተር አቶ ሰሎሞን አየለ ተናግረዋል፡፡
ፕሮግራም ዳይሬክተሩ አያይዘው ባለፈው ዓመት የተተከሉት ችግኞች አማካይ የመፅደቅ መመዘኛው 75.2 በመቶ መድረሱን ገልጸው፣ይህ ውጤት እንዲመጣ ያገዘው የተመጠነ እና ጥራት ያላቸው ችግኞች መተከላቸው፣በተከላ ቦታ የእርጥበት እቀባ ሥራዎች መሠራታቸው፣የምስጥ መከላከል ሥራ እና የተከላ ቦታዎች ከእንስሳት እና ከሰው ንክኪ ነጻ እንዲሆኑ በመደረጋቸው ነው፡፡