የግራቅዳም ታዳጊ ከተማ ጥልቅ ጉድጓድ የንጹህ መጠጥ ውኃ ተቋም ተመረቀ
በአመልድ ኢትዮጵያ የጆንስ ሪግ ዋሽ ፕሮጀክት በምስራቅ ጎጃም ዞን 5 ወረዳዎች (በጎዛምን ፣ ማቻከል ፣ ደብረ-ኤልያስ ፣ አነደድ እና ስናን ወረዳዎች) የውኃ ተቋም ግንባታ እና የስነ-ንፅህና ተግባራትን ይሠራል፡፡ ከቬልት ሁንገር ህልፈ በተገኘ 8.8 ሚሊዮን ኢሮ በጀት፣ በመንግሥት እና ማህበረሰቡ ትብብር ከ2009 እስከ 2016 ዓ.ም ድረስ 143,951 ሕዝብ የንፁህ መጠጥ ውኃ ተጠቃሚ ለማድረግ እየሠራ ነው፡፡
ፕሮጀክቱ በምሥራቅ ጎጃም ዞን፣ ማቻከል ወረዳ፣ የግራቅዳም ታዳጊ ከተማ ጥልቅ ጉድጓድ የንጹህ መጠጥ ውኃ ተቋም በአመልድ ኢትዮጵያ፣በመንግሥት እና በህብረተሰቡ (ጉልበት) ትብብር በ22 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው የውኃ ተቋም ተጠናቆ ሚያዚያ 23 ቀን 2015 ዓ.ም ተመርቋል፡፡ በፀሐይ ሀይል(ሶላር) የሚሠራው የውኃ ተቋሙ ከ10,000 በላይ የሚሆኑ የግራቅዳም ታዳጊ ከተማ እና የአካባቢውን ማህበረሰብ ተጠቃሚ ያደርጋል፡፡ የውኃ ጉድጓዱ 85 ሜትር ወደ ታች የተቆፈረ ጥልቅ ጉድጓድ፣ 7 የውኃ ማደያ (እያንዳንዳቸው 4 ውሃ መቅጃ ፎሴት ያላቸው) እና 2 የውኃ ማደያ (ለመንግሥት ተቋማት) በድምሩ 9 የውኃ ማደያ፣ቀድሞ በመንግሥት የተሠራ 12 የውኃ ማደያ፣ በድምሩ 21 ቦታዎች ላይ የውኃ ማከፋፈያ ግንባታዎች ተከናውነዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የግራቅዳም ታዳጊ ከተማ 120 ነዋሪዎች ቤት ለቤት የውኃ መስመር አስገብተው ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡
የአመልድ ኢትዮጵያ የውኃ፣ አካባቢ የግል ንጽህና እና የመስኖ ልማት ፕሮግራም ዳይሬክተር ደረጀ ተስፋሁን (ፒኤች.ዲ.) በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ እንዳሉት ከዚህ በፊት የቀበሌው ነዋሪዎች የመጠጥ ውኃ ችግር የነበረባቸው ሲሆን የውኃ ተቋሙ መገንባት የነዋሪዎችን የመጠጥ ውኃ ችግር የሚያቃልል ስለሆነ የውኃ ተቋሙ አግልግሎት ዘላቂ እንዲሆን እንዲሁም የውኃ አቅም የሚፈጥሩ የአካባቢ ጥበቃ ሥራ መሥራት እና በጥንቃቄ መጠቀም ይገባል ብለዋል፡፡ የምሥራቅ ጎጃም ዞን ምክትል ዋና አስተዳዳሪ አቶ መንበሩ ዘውዴ በበኩላቸው ፕሮጀክቱ በአራት ወራት በአጭር ጊዜ ተጠናቆ ለሕዝብ አገልግሎት መብቃቱ ለሌሎች ሥራዎች በአርአያነት የሚጠቀስ ተግባር ነው ብለዋል፡፡
የማቻከል ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታምሩ ዘውዴ በበኩላቸው የውኃ ተቋሙን ገንብቶ ለማጠናቀቅ የረጂ ድርጅቶች፣የአመልድ ኢትዮጵያ፣ የመንግስት እና የማህበረሰቡ ጠንካራ ቅንጅታዊ አሠራር ውጤት የታየበት ነው፡፡ በመሆኑም በጋራ ከሠራን ከዚህ በላይ የልማት ፕሮጀክቶችን ማሳካት ይቻላል ብለዋል፡፡
የግራቅዳም ታዳጊ ከተማ ነዋሪ አቶ እንዳልፈር መንግሥት ከዚህ በፊት የመጠጥ ውኃ ለማግኘት ሴቶችን በሌሊት ይዘን ምንጭ ወደአለበት ቦታ ሩቅ መንገድ ተጉዘን ውኃ ይዘን እንመጣ ነበር፡፡ አሁን ግን የውኃ ተቋሙ በመገንባቱ ችግሮችን ሁሉ ሙሉ በመሉ ስለፈታልን ረጂ ድርጅቶች፣አመልድ ኢትዮጵያ እና መንግስትን እናመሰግናለን ብለዋል፡፡
የውኃ ተቋሙ የምረቃ ስነ-ስርዓት ሲካሄድ የአመልድ ኢትዮጵያ የሚመለከታቸው ኃላፊዎች እና ባለሙያዎች፣ የምስራቅ ጎጃም ዞን እና ማቻከል ወረዳ የሚመለከታቸው ኃላፊዎች እና ባለሙያዎች እና የውኃ ተጠቃሚው ማህበረሰብ ተሳታፊ ነበሩ፡፡
በአመልድ ኢትዮጵያ የጆንስ ሪግ ዋሽ ፕሮጀክት በምስራቅ ጎጃም ዞን 5 ወረዳዎች ከ2009 ዓ.ም እስከ መጋቢት 2015 ዓ.ም ድረስ 130 የውኃ ተቋማትን (7 ጥልቅ ጉድጓዶች ፣ 99 መለስተኛ ጥልቅ ጉድጓዶች ግንባታ እና ጥገና፣13 የእጅ ጉድጓድ 11 ትልልቅ እና አነስተኛ ምንጮች ማጎልበት) ገንብቶ 100,131 ነዋሪዎችን የንጹህ ውኃ ተጠቃሚ አድርጓል፡፡ የፕሮጀክቱ ተጠቃሚዎችን ንጽህና ለመጠበቅ ለ16 ትምህርት ቤቶች የሚያገለግል 32 ብሎክ ዘመናዊ መፀዳጃ ቤት በመገንባት 16,070 ተማሪዎችን ተጠቃሚ አድርጓል፡፡ በተጨማሪም ለቀበሌ ማዕከላት 56 የሞዴል አየር ማስገቢያ ያላቸው የጉድጓድ መፀዳጃ ቤት ገንብቷል፡፡