አነስተኛ የመስኖ ልማቶች አነስተኛ ማሳ ላላቸው አርሶ አደሮች!
በእሱባለው ድረስ
የአማራ መልሶ መቋቋምና ልማት ድርጅት (አመልድ) ባለፉት 30 አመታት በክልሉ ውስጥ በርካታ የልማት ስራዎችን በማከናወን ድሃው ህብረተሰብ ህይወቱ እንዲለወጥ ጉልህ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ በተለይ ድርጅቱ በሚሰራባቸው የተፈጥሮ፣ የውሃ፣ የምግብ ዋስትናና ግብርና ሃብት ልማት እንዲሁም በወጣቶችና ስርዓተ-ፆታ የትኩረት መስኮች ባለፉት ዓመታት ውጤቶችን ማስመዝገብ ችሏል፡፡
የእንድራስ መስኖ ልማት ገጽታ(ቦረና፣ ለጋምቦ፣ ወግዲ)
በተፈጥሮ ሃብት ልማት ረገድ 604.6 ሚሊዮን ችግኝ በ104 ሺህ ሄ/ር በመትከል ከክልሉ የደን ሽፋን ዉስጥ 8% የሚሆነው ደን በድርጅቱ ቀጥተኛ የበጀት፣ የሙያና ተቋማዊ ድጋፍ እንዲሰራ አድርጓል፡፡ በመሆኑም ድርጅቱ እ.ኤ.አ የ2007 አገር አቀፍ የአረንጓዴ ጀግና ተሸላሚ ሆኗል፡፡
በውሃ ሃብት ልማት ዘርፍ እንዲሁ 5,200 ንፁህ የመጠጥ ውሃ ተቋማትን በመገንባት ከ2.6 ሚሊዮን በላይ የሆኑ የክልሉን ማህበረሰብ የንፁህ መጠጥ ውሃ ተጠቃሚ በማድረግ ከክልሉ የንፁህ መጠጥ ውሃ ሽፋን ዉስጥ ከ14 እስከ 16 በመቶ የሚሆነውን በመስራት ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ 14,201 ሄክታር መሬት የሚያለሙ 200 አነስተኛ የመስኖ ተቋማትን በመገንባትም 67,957 ቤተሰቦችን ተጠቃሚ አድርጓል፡፡ እ.ኤ.አ በ2009 የአገር አቀፍ የንፁህ መጠጥ ውሃና ንፅህና አጠባበቅ ስራዎች ምርጥ አፈፃፀም ተሸላሚ ሆኗል፡፡
በምግብ ዋስትናና ግብርና ልማት በ136.1 ሄ/ር ላይ የተተከለ 151225 የአፕል ችግኝ ለ7,739 ቤተሰቦች ተሰራጭቷል፡፡ በ637 ሄ/ር ላይ የተተከለ 177,016 የተዳቀለ ማንጎና ብርቱካን ችግኝ ለ13,025 ቤተሰቦች በማሰራጨት ተጠቃሚ እንዲሆኑ አስችሏቸዋል፡፡
አመልድ የመንግስትን የልማት ክፍተቶች በተለይ በዘላቂ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና አጠቃቀም፣ በመጠጥ ውሃ አቅርቦት፣ የግልና የአካባቢ ንጽህና፣ ተስማሚ የመስኖ ልማት አውታሮችን፣ የግብርና ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ቴክኖሎጅዎችንና አሰራሮችን እንዲሁም መሬት አልባና ስራ አጥ ለሆኑ ሴቶችና ወጣቶች የስራና የገቢ ምንጭ የሚሆኑ የእርሻና እርሻ ነክ ያልሆኑ የስራ ዘርፎችን በማስፋፋት ጉልህ ሚና አለው፡፡
አመልድ ጥራት ያላቸው አነስተኛ የመስኖ ግንባታዎችን በአጭር ጊዜ የሚያከናውነው ልዩ ባህሪው ከክልል እስከ ቀበሌ ድረስ አመራሩን እና አርሶ አደሩን በአጠቃላይ ህብረተሰቡን ንቁ ተሳታፊ በማድረጉ መሆኑ ነው፡፡ በዚህ ዓመትም 19 የመስኖ ተቋማትን በመገንባት ላይ ይገኛል፡፡
የክልላችን ብሎም የሃገራችን አርሶ አደሮች አነስተኛ ማሳ ይዞታ ያላቸው በመሆኑ በአነስተኛ ማሳቸው ከሁለት ጊዜ በላይ እንዲያመርቱ፣ በትንሽ ማሳ ብዙ ምርት እንዲያገኙና ይበልጥ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ለማስቻል አነስተኛ የመስኖ ልማቶች አነስተኛ ማሳ ላላቸው አርሶ አደሮች እጅግ ወሳኝ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ በመስኖ ሊለማ የሚችል ከ5.3 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት እንዳላት ጥናቶች ያመላክታሉ፡፡ ነገር ግን ሃገሪቱ ካላት እምቅ የመስኖ አቅም ሁለት ሚሊዮን ወይንም 38 በመቶ ብቻ እየለማ እንዳለ ነው የግብርና ሚኒስቴር መረጃ የሚያሳየው፡፡ በመስኖ የማልማት አቅማችንን ለማሳደግም በክልላችን መጠነ-ሰፊ የመስኖ ልማት አውታሮች እየተዘረጉ ይገኛሉ፡፡ የክልሉ መንግስት የሰጠውን ሃላፊነት ወስዶ አመልድ በአጭር ጊዜ ጥራቱን የጠበቀ ውጤታማ የመስኖ ግንባታዎችን በማከናወን ረገድ ግንባር ቀደም መሆን ችሏል፡፡ በ2006/2007 ዓ.ም እየገነባቸውን ከሚገኙ 26 ፕሮጀክቶች 22ቱን አከናውኖ ለውሃ ቢሮ እና ለተጠቃሚው አርሶ አደር እንዲሁም ለወረዳ ግብርና ጽ/ቤቶች አስረክቧል፡፡
የላይኛው ኳሽኒ መስኖ ልማት ገጽታ(ዳንግላ)
አርሶ አደር አያሌው ፈረደ በምስራቅ ጎጃም ዞን የማቻክል ወረዳ ግሩም የሳንቃት ቀበሌ ኗሪ ናቸው፡፡ አመልድ የጌደብን ወንዝ ጠልፎ ዘመናዊ የመስኖ ልማት በመገንባቱ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ መሆን እንደቻሉ ይናገራሉ፡፡ ገና በመስኖ መጠቀም የጀመሩት በ2005 ዓ.ም ሲሆን በ2006 ዓ.ም ሩብ ሄክታር በማትሞላው ማሳቸው 30 ኩንታል ድንች አምርተው ከ6 ሺህ ብር በላይ በመሸጥ ሰባ አምስት ዚንጎ ቆርቆሮ ቤት ሰርተዋል፡፡ የመስኖ ልማት በመጠቀማቸው በኑሯቸው እየተለወጡ እንደሚገኙ የሚገልጹት አርሶ አደሩ በማሳቸው የሚያልፈውን ውሃ በመጠቀም ሌትም ቀንም ሰርተው ሃብት እንደሚያፈሩ አመልድ ባለሙሉ ተስፋ አድርጓቸዋል፡፡
የጌደብን መስኖ ተጠቅመው የድንች ምርት ሲያፍሱ/ማቻክል/
በምዕራብ ጎጃም ዞን ከ15.5 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ የተገነባው የካሎ መስኖ 262 ሄክታር መሬት የሚያለማ ሲሆን 564 አባውራና እማዎራ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ አድርጓል፡፡ የአካባቢው አርሶ አደሮች ማሳቸውን ለመስኖ እያዘጋጁ ናቸው፡፡ አርሶ አደር ጋሹ እጅጉ በወምበርማ ወረዳ አባና ሰባዳር ካሎ ቀበሌ ኗሪ ናቸው፡፡ አርሶ አደርሩ የካሎ ወንዝ ለመስኖ በመዋሉ የተሰማቸውን ደስታ " አፈር ሸርሽሮ እኛም በወንዙ እየተበላን ብዙ ዓመታትን አስቆጥረናል፡፡ ዛሬ ግን ጥፋት ሲያደርስ የኖረው ወንዝ የልማቱ አጋር አመልድ ወንዙን ጠልፎ ዘመናዊ መስኖ በመገንባት ለዚህ አበቃኝ፤ ይህን ሁሉ ያገኘነው ከመሰንበት ዳርቻ ነው፡፡ ዛሬ ይመስገነው አይለቅበት ድንች፣ ሽንኩርት፣ ጎመን እየሸመትን እንመገብ የነበረው በአሁኑ ሰዓት ራሳችንን ከመቻል አልፈን ለገበያ ልናቀርብ ሌት ተቀን እየሰራን እንገኛለን፡፡" በማለት ነበር የገለጹት፡፡
አመልድ በ8.4 ሚሊዮን ብር በአዊ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን በባንጃ ወረዳ የቡችክሲ ዘመናዊ መስኖ አውታር ገንብቷል፡፡ ይህ ዘመናዊ መስኖ ከ230 ሄክታር መሬት በላይ የሚያለማ ሲሆን 1360 አባውራና እማዎራ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ አድርጓል፡፡ ከተጠቃሚዎች መካከል የአስኩና አቦ ቀበሌ የ7 ልጆች አባት አርሶ አደር ታደለ ፈንታ አንዱ ናቸው፡፡ በመስኖ ያለሙትን ገብስ እያጨዱ ነበር ያገኘናቸው፡፡ የቡችክሲ ዘመናዊ መስኖ አውታር በመገንባቱ በስፋት መስኖ ልማት ላይ እንደገቡ ይናገራሉ፡፡ በፊት በባህላዊ ለማልማት ቢሞክሩም እዚህ ግባ የሚባል እንዳልነበር ገልጸው በአሁኑ ሰዓት ወንዙ በአግባቡ ተጠልፎ በመንደራቸው በመግባቱ ከሁለት ጊዜ በላይ እያለሙ ይገኛሉ፡፡ በፊት ወደ መሬት የሚሰርግና በከንቱ የሚባክን ውሃ፣ ከፍተኛ ጉልበት እና ጊዜ ይጨርሱ ነበር፡፡ በአሁኑ ሰዓት ግን ችግሮች ስለተቀረፉ ተመርቶ የማይታወቁ ሰብሎችን እያለሙ ይገኛሉ፡፡ ከደረሱት ሰብሎቻቸውም በአማካይ ገብስ 10 ኩንታል፣ ድንች 8 ኩንታል፣ ሽንኩርት 8 ኩንታል ምርት እንደሚያገኙ ይጠብቃሉ፡፡
ቡችክሲ መስኖ ልማት(ባንጃ)
በኦሮሞ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን የሙጢፈቻ አነስተኛ የመስኖ ልማት ከ25 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ የጅሌ ጥሙጋ እና ጥቂት የኤፍራታና ግድም ወረዳዎችን ተጠቃሚ አድርጓል፡፡ ፕሮጀክቱ 400 ሄክታር መሬት የሚያለማ ሲሆን 1339 አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ አድርጓል፡፡ የሙጢፈቻ መስኖ ልማት ከኢኮናሚያዊ ፋይዳው ባሻገር ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ችግሮችንም ቀርፏል፡፡ በተለይ ከተለያዩ የወሎ ወረዳዎች በሰፈራ የመጡትና ለረጅም ዓመታት ሲጋጩ የኖሩት የኤፍራታና ግድም እና የጅሌ ጥሙጋ ህዝቦች ችግራቸውን ቀርፎላቸዋል፡፡ አመልድ ወደ ግንባታ ከመግባቱ በፊት ህብረተሰቡን አወያይቶና አሳምኖ ሲፈስ የነበረውን የሰው ደም በጎችን በማረድ ለእርቅ አብቅቶ በአንድ መሶብ እንዲቀርቡ አድርጓቸዋል፡፡ የአካባቢው ኗሪዎችም ፊታቸውን ወደ ልማት ካዞሩ ሰነባብተዋል፡፡ አርሶ አደር አያሌው ፍስሃ በኤፍራታን ግድም ወረዳ ጀዋሃ ኔጌሶ ቀበሌ ኗሪ ናቸው፡፡ በነጌሶ ጎጥ የደረሰ የጤፍ ማሳቸውን ከወፍ እየተከላከሉ ነበር ያገኘናቸው፡፡ በአካባቢው መስኖ ልማት የጀመረው ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ ሲሆን በተለይ በዘመናዊ መንገድ በመገንባቱ ሽንኩርት፣ በቆሎ፣ በርበሬ፣ ማሾና ጤፍ እያለሙ ይገኛሉ፡፡ አርሶ አደሩ " ካሁን በፊት የዓመት ቀለቤን መሸፈን ባለመቻሌ የቀን ስራ እየሰራሁ ነበር የምኖረው፡፡ ነገር ግን መስኖውን ስለጠለፈልን የቀን ስራውን ትቼ ሙሉ ጊዜየን በግብርና ልማት ላይ አውየዋለሁ፡፡ በመሆኑም የምግብ ፍጆታየን በመሸፈን በቀጣይ ሃብት የማፈራበትን እድል አመልድ ፈጥሮልኛል፡፡" ብለዋል፡፡
በመስኖ የለማ ጤፍ /ሙጡፈቻ/
ድርጅቱ የክልሉን አርሶ አደር የመስኖ ልማት አልምቶ ህይወቱ እንዲለወጥና ምርትና ምርታማነትን የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥል የመንግስት፣ መንግስታዊ ያልሆኑና የአጋር አካላት ተሳትፎ ድርሻ ወሳኝ በመሆኑ በትብብር ለውጥ እናምጣ መልዕክታችን ነው፡፡