ዜና
ሁሉን አቀፍ የጤና፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ልማት ፕሮጀክት ስኬቶች በከፊል! በአመልድ ኢትዮጵያ ሁሉን አቀፍ የጤና ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ልማት ፕሮጀክት ሆፕ ኤንድ ሂሊንግ ኢንተርናሽናል ከተባለ ግብረሰናይ ድርጅት ባገኘው 92 ሚሊዮን ብር በጉና በጌምድር እና አንዳቤት ወረዳዎች 1 ሺህ 907 በድህነት የሚኖሩ ወገኖችን (የአካል ጉዳተኞችንና ሴቶችን ጨምሮ) ህይዎት ለመለወጥ በተመረጡ አስራ አምስት/15/ ቀበሌዎች በኑሮ ማሻሻያ እና በጤናው ዘርፍ እየሰራ ይገኛል። ይህ የ5 ዓመታት ፕሮጀክት እ.ኤ.አ ከ2019-2023 በኑሮ ማሻሻያ ዘርፎች የተሻሻሉ የሰብልና የእንስሳት ዝርያዎችን፣ አነስተኛ የመስኖ አውታር ዝርጋታ እንዲሁም በጤናው ዘርፍ የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት፣ የትራኮማ መከላከል ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል፡፡ ለአብነት ዓይን ሲፈዝ፣ እግር ሲደነዝዝ ጧሪ ያገኙትን አዛውንት አቶ አሰፋ ንጉሴን ታሪክ መለስ ብለን እንቃኛለን፡፡ አቶ አሰፋ ንጉሴ በደቡብ ጎንደር ዞን አጸደ ማርያም ቀበሌ ሸሆች መንደር የሚኖሩ የ60 ዓመት አዛውንት ሲሆኑ 4 ወንዶችና 3 ሴቶች ልጆች አሏቸው፡፡ እኒህ አባት ኑሯቸውን ለማሸነፍ የሚታትሩ አርሶ አደር ነበሩ፡፡ ይሁን እንጅ እንደ አለመታደል ሆኖ በ45 ዓመታቸው ባልታወቀ ምክንያት እግራቸው እንደወትሮው መራመድ/መንቀሳቀስ ባለመቻሉ የአካል ጉዳተኛ ሆኑ፡፡ አቶ አሰፋ ወደ አዲስ አበባ በማቅናት አለርትና ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ውስጥ ህክምና ሲከታተሉ ቢቆዩም እግራቸው ወደቀድሞ የአካል ሁኔታ ሊስተካከል አልቻለም፡፡ አቶ አሰፋ ረጅም ርቀቶችን ለመራመድ ከብረት የተሰራ መደገፊያ ክራንች እንዲኖራቸው ቢመኙም በዋጋው ውድነት ሳቢያ ማሟላት አልቻሉም። በዚህ ምክንያት ከእንጨት የተሰራ ክራንች በመጠቀም በመንደሩ ይንቀሳቀሳሉ፡፡ የአካል ጉዳት ከደረሰባቸው በኋላም አቶ አሰፋ ሙሉ በሙሉ በልጆቹ ላይ የኢኮኖሚ ጥገኛ ሆኑ፡፡ አመልድ የኑሯቸውን ሁኔታ በመረዳት ሆፕና ሂሊንግ ኢንተርናሽናል ከተሰኘ ግብረሰናይ ድርጅት ባገኘው የገንዘብ ድጋፍ የአርሶ አደሩን ህይወት ለማቃናት ስራይጀምራል፡፡ ቀደም ሲል ሲቸገሩ አዲስ አበባ ለህክምናና ለዳቦ ይለምኑ እንደነበር የሚናገሩት አዛውንት አሁን አመልድ 3 በጎችን (2 እናቲትና 1 የዋሸራ አውራ በግ) እንዲሁም እርሳቸው 3 በግ በማቅረብ በእርባታ ኑሯቸውን እንዲደጉሙ ምክንት ሆኗቸዋል፡፡በአጠቃላይ በጎቹ በቁጥር 11 ደርሰዋል፡፡ በአሁኑ ሰዓት ከልጆቹ ጥገኝነት ወጥተው አነስተኛ መሬታቸውን በማከራየት በጎችን እያረቡ ይገኛሉ፡፡ አቶ አሰፋ በኑሯቸው ደስተኛና ባለተስፋ ሆነዋል፡፡ በመኖሪያ ቤታቸው አቅራቢያ በመንቀሳቀስም የሚጦሯቸውን በጎቻቸውን ይንከባከባሉ፡፡ በበግ እርባታ ኑሯቸው በደስታ የተሞላው አዛውንት-አቶ አሰፋ ንጉሴ! |
|